
የማይደፈረው ዳኛ ጌታቸው ገ/ማርያም ‼️ ያልተከፈለው የ60 ዓመት አገልግሎት ‼️ የ20ኛ ዓመት የፌዴሬሽናችን ክብረ በዓል ላይ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ ውስጥ ስማቸው በደማቁ የታሪክ ማህደር ላይ ተፅፎ የሚገኘውን ለ60 ዓመታት ያህል ከተጫዋችነት እስከ ኢተርናሽናል አልቢተርነት ከኮሚሽነርት እስከ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳኝት በማገልገል በስፖርት ቤተሰቡ ዘንድ በክብር የሚታወሱትን ኢንተርናሽናል አልቢትር ጋሽ ጌታቸው ገ/ማርያምን የክብር እንግዳችን አድርገን የጋበዝን መሆኑን ስንገልፅ ኩራትም ክብርም ይሰማናል ። ጋሽ ጌታቸው የእግር ኳስ ሕይወታቸው የሚጀምረው ከኦሜድላ ክለብ ሲሆን ድንቅ የተከላካይ መስመር ተጫዋች ነበሩ ። ከኦሜድላ ቀጣይ ክለባቸው አንጋፋው የድሬደዋው ጨርቃጨርቅ ክለብ ሲሆን በወቅቱ ማለትም 1953 ኢትዮጵያ ባዘጋጀችው እና ብቸኛው ሻምፒዮን መሆን በቻለችበት 3ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ከተመለመሉት 35 ተጫዋቾች ውስጥ የተካተቱ ሲሆን ቡድኑም የ3ኛውን አፍሪካ ዋንጫ ሲያነሳ ቤተመንግስት ተጋብዘው ከቀዳማዊ ሃ/ስላሴ ሽልማት ወስደዋል ። ጋሽ ጌታቸው ወደ ዳኝነቱ ሙያ እንዴት እንደገቡ ሲገልፁ ከድሬደዋ ጨርቃ ጨርቅ ከሉቻኖ እና መንግስቱ ወርቁ ጋር የአሰልጣኝነት ኮርስ ለመውሰድ ነበር የመጣሁት ግን በሚያስገርም ሁኔታ “ጋሽ ይድነቃቸው ወደ እኔ መጥቶ አንተ አሰልጣኝ ሳይሆን ዳኛ ነው መሆን ያለብህ አለኝ” ይላሉ የዳኝነት ስልጠናየን የጨረስኩት ቶሎ ቶሎ ነው 1ኛ 2ኛ እና ፌዴራል ዳኛ የሆንኩት በፍጥነት ነው ይላሉ ። 1957 ካይሮ ላይ ግብፅ እና ቱኒዚያን በማጫወት የጀመረው ኢንተርናሽናል አርቢትርነት ሕይወቴ ለመቁጠር የሚከብዱ በየሀገሩ እየተዘዋወርኩ በርካታ ጨዋታዎችን በብቃት በመወጣት የሀገሬን ባንዲራ ከፍ ብሎ እንዲውለበለብ አድርጌያለው ይላሉ ። አልቢትር ጋሽ ጌታቸው ሙያቸውን እና ስፖርቱን በንፅህና እና በታማኝነት ማገልገላቸውን ብዙዎች ይመሰክሩላቸዋል ። ሀማሴን እና ኤሌትሪክን አስመራ ላይ ባጫወትኩበት ወቅት የሀማሴን ክለብ አመራሮች 30ሺ ብር እንስጥህ ብለውኝ የነበረ ሲሆን እኔ ግን ብሩ በወቅቱ ብዙ የነበረ ቢሆንም አላታለለኝም ጋሽ ይድነቃቸውም የጨዋታውን ሪፖርት ሲያይ ከልብ ኮርቶብኛል ሲሉ አጫውተውናል አልቢትር ጋሽ ጌታቸው በዳኝነት ዘመናቸው ሁሌም የተሰጣቸውን እምነትና ሀገራዊ ሃላፊነት በብቃት በመወጣት ከራሳቸው አልፈው ሕዝባቸውን ያኮሩ ባንዲራችን ከፍ ብላ እንድትውለበለብ የድርሻቸውን የተወጡ ድንቅ የሙያው አባት ናቸው ። የሞቃድሾው ጨዋታ ውጥረት ❗️ ወቅቱ 1968 ነው ኢትዮጵያ እና ሶማልያ ወደ ጦርነት የገቡበት ከባድ ወቅት ቢሆንም ፊፋ ግን እኔን በመሃል ዳኝነት ሶማልያ ከኒጀር ሞቃድሾ ላይ እንዳጫውት መረጠኝ ሁኔታው ለደህንነቴ አስጊ ስለሆነ ጋሽ ይድነቃቸው ከወቅቱ የውጭ ጉዳይ ሚንስትር ኮረኔል ጎሹ ወልዴ ጋር በመሆን ሁኔታውን ለፕሬዝደንት መንግስቱ ሃ/ማርያም ቀርበን ያስረዳን ቢሆንም ምንም ነገር መፍጠር አልቻልንም ። የኔ ከጨዋታው መቅረት እኔም ላይ ሆነ ኢትዮጵያ ላይ የፊፋ ቅጣት ያስከትልብናል ስለዚህ ሳልወድ በግዴ ሞቃድሾ ሄጄ አጫወትኩ ይላሉ ። በወቅቱ ሶማልያ ውስጥ የኢትዮጵያን ባንዲራ እየረገጡ የሚጨፍሩ ደጋፊዎች ባይም እኔ ግን ባንዲራዬን ሳይወዱ በግዳቸው በክብር ተሰቅሎ እንዲውለበለብ አድርጌያለው በማለት ትዝታቸውን አጋርተውናል ። ደፋሩ እና ኮስታራው አልቢትር ጌታቸው ገ/ማርያም ትልቁን የኢትዮጵያ ደርቢ ጊዮጊርጊስ ከ መቻል የፍፃሜ ጨዋታ ለ5 ተከታታይ አመታት በብቸኝነት እና በብቃት እንዳጫወቱ ታሪክ ይዘክራል ። ከዳኝነት ሲሰናበቱም ላበርክቶዋቸው በ1986 በብቸኝነት የእድሜ ልክ የስታድየም ነፃ መግቢያ ከእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ ተበርክቶላቸዋል ። አልቢትር ጋሽ ጌታቸው ዳኝነት ካቆሙ በዋላም ቢሆን በበርካታ ሃላፊነት ቦታዎች እስከ 2009 ድረስ ስፖርቱን በፅናት አገልግለዋል ። ⭕️በኮሚሽነርነት በርካታ ዓመታትን ⭕️የአዲስ አበባ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዝደንት ⭕️የጠቅላይ አርቢትር ኮሚቴ ሰብሳቢ ⭕️የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ስራ አስፈፃሚ አባል ነበሩ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን እንዲሁም በስፖርቱ ዙርያ ያሉ ተቋማት አልፎ አልፎም ቢሆን የቀድሞ ተጫዋቾች እና አሰልጣኞን ለማስታወስም ሆነ ድጋፍ ለማድረግ ይሞክራሉ እንጂ እንደነ ጋሽ ጌታቸው ላሉ ካለበቂ ክፍያ እና ጥበቃ ከሀገር ሀገር እየተንከራተቱ ለስፖርቱ እድገት ላበረከቱት አስተዋፅኦ ምንም አይነት ድጋፍ ሲያደርጉላቸው አላየንም ። ይሄ እንደ አንድ ስፖርት ማሕበር ያሳዝነናል እንዲታረምም እንፈልጋለን ። እነሆ ግዜው ደርሶ ፌዴሬሽናችን 20ኛውን ዓመት ክብረ በዓል አብረውን እንዲያከብሩ እና እኛም ለሰጡን ሁሉ አገልግሎት ከፍ አድርገን እንድናመሰግናቸው ኢንተርናሽናል አልቢትር ጌታቸው ገ/ማርያምን የክብር እንግዳ አድርገን ስንጋብዝ በድጋሚ እጅግ ደስተኞች መሆናችንን ልንገልፅ እንወዳለን ። በሰላም ፍራንክፈርት ላይ ያገናኘን 🙏 ESCFE